Showing posts with label አማርኛ. Show all posts
Showing posts with label አማርኛ. Show all posts

Wednesday, August 24, 2016

ወልቃይት እንኳን ህዝቡ መሬቱም ትግራዋይ ነው




1.    መግብያ


የኢትዮጵያ ክልሎች አወቃቀር ሁሉንም ኢትዮጵያውያን አብረውና ተከባብረው እንዲኖሩ የሚያስችል ቢሆን ደስ ይለኝ ነበር፡፡በተለያዩ ወቅቶች ኢትዮጵያን ያስተዳደሩ ገዢዎች ለህዝቡ ምቾት ሳይሆን ለራሳቸው በሚመች መልኩ ሃገሪቱን ሲስተዳድሩ እንደነበር ይታወቃል፡፡የአሁን መንግስትም ለራሱ በሚመቸው መልኩ እያስተዳደራት ይገኛል፡፡ሆኖም ግን ብዙ ሰዎች፣ በተለይም የጎንደር ተወላጆች በደርግና በአጼ ሃይለስላሴ ወደ ነበረው አከላለል ካልተመለስን እያሉ ይገኛሉ፡፡ይህ ጥያቅያቸው እንደ ድሮው ቋንቋው አማርኛ፣ ሰንደቅ ዓላማው ልሙጡ አረንጓዴ፣ ብጫ ቀይ እንዲሆን ይፈልጋሉ፡፡
ከዚህ ጋር ተያይዞ ግን ወልቃይትና ፀገዴም ወደ ጎንደር ካልተካለሉ እያሉ ይገኛሉ፡፡ጥያቄው የተነሳበት ቦታ፣ታሪካዊና ነባራዊ ሁኔታ ግን አሁን ካለው አከላለል አንፃር ወደ መግባባት ሳይሆን ወደ ንትርክ የሚያመራ ነው፡፡ወልቃይት በአማራ ክልል ስር ስለነበር ወደ አማራ ክልል ይመለስ የሚሉት ጥያቄ ቢዘሁ የሚያበቃ አይመስለኝም፡፡ ቤንሻንጉል ጉሙዝም ወደ አማራ ካልተካለለ ሊባል ይችላል፡፡ ሲጀመርም የጌቶች ትእዛዝ እንጂ የህዝብ ጥያቄ ነው ለማለት ይከብዳል፡፡

ሁለት እረኞች ራቅ ብሎ በሚገኘው አንድ ትልቅ ቋጥኝ ላይ የሆነ እንስሳ አሻግረው ያያሉ፡፡
አንዱ ፡-እዛጋ ያለው እንስሳ ምንድነው?

Friday, April 22, 2016

የእኛ ሃገር ጉድ አይልቅም!!!


ዛሬ ጥዋት ፋና ብሮድካስቲንግ የዘገበው አስገራሚ ዜና ነው፡፡ሰላም ሐጎስና ሰላም ደሞዜ የተባሉ ታማሚዎች ለህክምና ወደ ዘውዲቱ ሆስፒታል ይመጣሉ፡፡ሰላም ሐጎስ የሃሞት ጠጠር ሕመምተኛ ስትሆን የቀዶ ሕክምና ቀጠሮዋ ደርሶ ወደ ሆስፒታሉ ታመራለች፡፡ሰላም ደሞዜም የቀዶ ሕክምና ቀጠሮ ነበራት፣ የእንቅርት እጢ ለማስወጣት፡፡

የሆነው ግን እጅግ የሚያሰደነግጥ ነው፡፡ሰላም ደሞዜ የእንቅርት(የአንገት እጢ) ቀዶ ጥገና ብቻ ሊደረግላት ሲገባ የሃሞቷም ጭምር ተቀደደች፡፡ከኤንስቴዥው ስትነቃ ጨኾች፤ የታመምኩት እንቅርቴ ሆኖ ሳለ ሆዴ ለምን ቀደዳችሁኝ ብላም ጠየቀች፡፡ነርሶቹ ‹‹ችግር የለውም ተረጋጊ፤ እንዳውም ተጨማሪ ቀዶ ጥገና በነፃ አድርገንልሻል›› አሏት፡፡ባትስማማም ሰሚ አላገኘችም፡፡

ሰላም ሐጎስ በበኩሏ እንደጠበቀችው የእንቅርት እጢ ለማስወጣት የሚደረገው ቀዶ ጥገና ሳይሆን የሃሞት ጠጠር ሊወጣላት መሆኑን ተነገራት፡፡አይደረግም አለች፡፡አራጆቹ አልተበገሩም፣ በሐይል ሊቀዷት ተዘጋጁ፡፡ እርይታዋን አቀለጠቸውና ወጣች፡፡

ይህን በተመለከተ የሐኪሞቹ ተቆጣጣሪ ማነጋገር እንደሚፈልጉ ተናገሩ፡፡ አርፋችሁ ተቀመጡ የሚል መልስ ተሰጣቸው፡፡የፋና ጋዜጠኛ እንደዘገበው ከሆነ የዘውዲቱ ሆስፒታል መዲካል ዳይረክተርም ተፈልጎ ሊገኝ አልቻለም፤ ስብሰባ ላይ ናቸው በሚል ሰበብ፡፡

ይህ ወሬ፣ የሙያ ስነምግባርና የአካዳሚክ ብቃት ሳይኖራቸው በፎርጅድ ወረቀት ሰው የሚያርዱ ‹‹ሓኪም›› ተብየዎችን ይባስ እንድፈራቸው አደረገኝ፡፡ኧረ እንዳውም ሐኪም የሚሉት ሁሉ እንድጠራጠር አድርጎኛል፡፡

ለምን ቢባል እንደዚህ ዓይነት አሰቃቂ ክስተቶች መደጋገማቸው ስለበዛ፡፡የታመመው እግሩ ሊቆረጥ ወደ ጳውሎስ ሆስፒታል ያመራው ታካሚ ጤነኛው እግሩ መቆረጡን አስታውሳለሁ፡፡

Monday, April 18, 2016

ብዙ የተወራላቸው የኢትዮጵያ የሃገር የመከላከያ ሰራዊትና የድህንነት ተቋማት የት ገቡ?



የትግራይ ህዝብ ሲተርት ‹‹ጨጓርያ ከልብስ ኣሎ እናበልኻዮ ይመውት›› ይላል፡፡ፀጉራም ውሻ አለ እያሉት ይሞታል ማለት ነው፡፡ፀጉራም ውሻ መታመሙንና ምንኛ እንደከሳ ማወቁ አዳጋች ነው፤ ለተመልካቹ ሁሌም ገዝፎና ወፍሮ ስለየሚታየው፡፡እናም ሲሞት ድንገት የሞተ ያህል ምን ነካው? ያስብላል፡፡የሃገራችን መከላከያ ሰራዊት በተለያዩ የአፍሪካ ሃገሮች ስኬታማ የሚባሉ የሰላም ማስከበር ስራዎች በማከናወኑ በተደጋጋሚ ሲወደስና ሲሞገስ ይስተዋላል፡፡

በአሁኑ ሰዓት እንኳን ሁለቱም ሱዳኖች ባፋጠጠችው በአብዬ ግዛት ስላም በማስከበር ላይ እንደሚገኝ ይታወቃል፡፡በሃገረ ሶማልያም አልሻባብን እየተፋለመ እንደሚገኝ የሚታወስ ነው፡፡በቴክኖሎጂ ዘርፍም ከፍተኛ የሆኑ እምርታዎች በማስመዝገብ ላይ መሆኑን በመንግስት ሚድያዎች ተዘግቧል፡፡ከተወሰኑ ዓመታት በፊት የሃገር መከላከያው ባዘጋጀው ዓውደ ርእይ ሰው አልባ በራሪ አካላት (ድሮንስ) እስከ ማምረት እንደ ደረሰ ተነግሮን ነበር፡፡

ሌላው የሃገር ድህንነት ተቋሙ በአወቃቀርም ሆነ በቴክኖሎጂ አጠቃቀሙ የተራቀቀ በመሆኑ የሃገራችን ሰላምና መረጋጋት ማረጋገጡን ሲለፈፍ ነበር፡፡ኬንያ የአልሻባብ ተደጋጋሚ ጥቃቶች ለማስተናገድ ስትገደድ፣ ዩጋንዳና ጁብቲም የጥቃቱ ሰለባ ሲሆኑ ኢትዮጵያ ምንም ዓይነት ጥቃት ያልደረሰባት የድህንነትና የመከላከያ ሃይላችን አስተማማኝ ስለሆነ ነው የሚሉ ክርክሮች መስማትም አዲስ አይደለም፡፡

በቅርቡ ሙርሌ የተባሉ የደቡብ ሱዳን ጎሳ ታጣቂዎች በጋምቤላ ክልል ውስጥ በሚገኙ የኑዌር ተወላጆች ያደረሱት ጥቃትና አፈናን ጨምሮ በሃገራችን የተሰነዘሩት ተደጋጋሚ ጥቃቶች ስንመለከት ግን እውነታው ሌላ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡በኤርትራ አዋሳኝ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን በሻዕብያ መንግስትና ኤርትራ በመሸጉ አማፂ ቡድኖች በተደጋጋሚ ይታፈናሉ ይገደላሉ፡፡

በሃገር ውስጥም ግጭት በተከሰተ ቁጥር በመቶዎች የሚቆጠሩ ዜጎች ህይወት ማለፉንና ደም መፍሰሱ አልቀረም፡፡ፖሊስ፣ መከላከያና ድህንነት ዘመናዊ የሆኑ ቴክኖሎጂዎችን ተጠቅመው ግጭቶች ከመከሰታቸው በፊት ማክሸፍ፣ ግጭቶቹ ከተከሰቱም የሰው ህይወትና ንብረት ሳይወድም በቀላሉ መቆጣጠር ሲገባቸው በተደጋጋሚ ህይወትና ንብረት ሲወድም ይስተዋላል፡፡እናም እነዚህ ተቋማት የተሸከሙት ክብርና ዝና ከልሏዋቸው አሉ ብለን ስንኩራራ አሸልበው እንዳይሆን ያሰጋል፡፡የስጋቴ ምንጭ የሚከተሉት ናቸውና አንድ በአንድ እንያቸው፡፡

የአየር ክልላችን ክፍተት ያጋለጡ ክስተቶች

Friday, March 25, 2016

ከምርቃቱ በፊት የማስታወቅያ ስራውን በስኬት ያጠናቀቀው ቤዛ ፊልም


ቢዛ ፊልም
በሬድዮና ቴሌቪዥን ዝግጅቶች የምናውቀው ብርሃነ ንጉሰ ወደ ፊልም ኢንዲስትሪው በይፋ መቀላቀሉን የሚያበስር ወሬ ይዞ ብቅ ብሏል፤ቢዛ ፊልም፡፡በፖስተሩ ላይ ያሉ ተዋናዮች ስመለከት የልጅነት ጀግኖቼን አስታወሱኝ፡፡እነ ሻምበል ሮማን፣ እነ ጓል ዓይነታ፣ እነ ሲሳይ ገበል፣ እነ ጉማ፣ እነ ቀጭ ሕርሙ፣ ሽላ መረብ…

በተላይ ያቺ ሰላም ተስፋይ የሚሏት ልጅ ሳይ በጣም ነው የደነገጥኩት፡፡ያቺ ገና ህፃን እያለሁ ‹‹ማንጅስ፣ ይህ ትግል ከግቡ የምታደርሱት እናንተ ናችሁ፤ ስጋ ብፆት›› የሚል ትንቢት የነገረችኝ ሻምበል ሮማን በአካል ድቅን አለችብኝ፡፡በህይወት ትኑር አትኑር አላውቅም፡፡ምስሏና አነጋገሯ ግን በህይወት እስካለሁ ድረስ ከእኔ ጋር ይኖራል፡፡ይህ እውነታ የእነ እንትና ጭሆት ሊፈቀው አይችልም፡፡በጭራሽ!

እነ ሻምበል ሮማን የታገሉት የደርግ ስርዓት አሁን ባለው ስርዓት ለመተካት እንዳልነበረ በእርግጠኝነት መመስከር እችላለሁ፡፡ለዛም  ነው ‹‹ትግሉን ከግቡ የምታደርሱት እናንተ ናችሁ›› ያለችኝ፡፡በእቅፏ አድርጋ ስስ ፀጉሬን እያሻሸች፣ በራሽን መልክ ተሰጠቻት ዳቦ በሻይ ለእኔ አስረክባ፡፡ይህ መሆኑን ሁለት ጠላቶች እንዳፈራ ግድ ብሎብኛል፡፡ባንድ በኩል ሁሉንም ጠቅልሎ ሲያበቃ፣ ሁሉንም እንድናጣ የደረገን ስርዓት መታገል ይኖርብኛል፡፡በሌላ በኩል ደሞ ይህ ስርዓት ሙሉ በሙሉ የጠቀለለውን ሁሉ በሃይል ለመረከብና ‹‹የጠቅላይ አግላይ›› አዙሪቱን ለማጦዝ የተዘጋጁትን መፋለም እንዳለብኝ ያሳብቃል፡፡

Monday, March 7, 2016

‹‹ከአሜን ባሻገርን›› አሜን ብዬ የማልቀበልበት ምክንያቶች (II)

ምክኒያታዊነትና ሰብአዊነት

‹‹ከአሜን ባሻገር›› በ246 ገፆች የተሰደሩ 20 መጣጥፎች ይዛለች፡፡የመፅሐፏ ሽፋን ልዩ ምልክት ብስኪሌት(ባይሲክል) ስትሆን የሳይክሏ የፊትጎማ የዳግማዊ ምኒልክ ምስል ያለው ሳንቲም፣ እንዲሁም የኋለኛው ጎማ በ2002 ዓ.ም ታትሞ በማገልገል ላይ ያለው ብረቱ የአንድ ብር ኖት ነው፡፡

የሳይክሏ በዚህ መልኩ መቅረብ የሚጠቁመው ድሮና ዘንድሮ የኢትዮጵያ የማይነጣጠሉ ሁለት ገፅታዎች መሆናቸውን ለመጠቆም ይመስላል፤ ‹‹የኋላው ከሌለ አይኖሩም የፊቱ›› እንዲሉ፡፡ወይም ድሮ ያለዘንድሮ መንቀሳቀስ አይችልም የሚል እሳቤ ለማስረገጥ ነው፡፡አንድ የርቀት ዝላይ ስፖርተኛ ወደፊት መዝለል የሚችለው ርቀት ወደ ኋላ ተንደርድሮ የሮጦው ፍጥነት ወሳኝ የሆነውን ያህል፣ የዛሬው የሃገራችን እርምጃም ትናንት ስትራመደው በነበረው ፍጥነት ይወሰናል፤ አሳማኝ ነው፡፡

ደራሲው ድሮና ዘንድሮ ምንኛ እንደተዋኸዱ ሲገልፅ፣‹‹የዛሬው ዘመን ምን ቢታገል ካለፈው ዘመን ተለይቶ ጎጆ መውጣት አይችልም፡፡ያለፈው ዘመንና የዛሬው ዘመን እንዳይፋቱ ሆነው ተቆራኝተዋል፡፡አንዳንዴ ሳስበው፤ ‹‹ዘንድሮ›› በሚለው ቃል ውስጥ ‹‹ድሮ›› የሚለው ቃል መገኘቱ ባጋጣሚ አይመስለኝም፡፡›› ብሏል በገፅ 9 ላይ፡፡እዚ ጋ፣ አንድ ጥያቄ መነሳት አለበት፤ እሱም፣ ድሮና ዘንድሮ ይህን ያህል የተቆራኙ ከሆኑ ዘንድሮን ከድሮ ነጥለን መተቸት እንችላለን ወይ? የትናንቱ ታሪካችን ያተነፈሰው ጎማ፣ ዛሬ በፈለግነው ፍጥነት ሊያንቀሳቅሰን ካልቻለ ዘንድሮን ነው መኮነን ያለብን? ደራሲው፣ እስከ መቼ ድረስ የነበረውን ታሪካችን ነው ‹‹ድሮ›› እያለ የሚጠራው? ‹‹ዘንድሮ›› የሚለውንስ?

Thursday, March 3, 2016

‹‹ከአሜን ባሻገር››ን አሜን ብዬ የማልቀበልበት ምክንያቶች (I)



ስሜት


በውቀቱ ስዩም ዘመኑ ካፈራቸው ደንቅ የስነ ፅሑፍ ሰዎች አንደኛው ነው፡፡ በቅርቡ ‹‹ከአሜን ባሻገር›› የተሰኘው መፅሐፉን ለሕትመት ማብቃቱን ስሰማ ደስታየ ወደር አልነበረውም፡፡ የእርሱ መፅሐፍ ለማንበብ የነበረኝ ጉጉት የላቀ ስለነበረም የመጀመርያው እትም ገዝቼ ማንበብ ችያለሁ፡፡

የበውቀቱ ሽሙጦች ባነበቡኩኝ ቁጥር እንባየን መቆጣጠር እስኪያቅተኝ ድረስ በሳቅ እንፈረፈራለሁ፡፡በመሆኑም የሆነ ደባሪ፣ረዥምምምና ጨፍጋጋ ጊዜ መግደል ሲያስፈልገኝ ‹‹መውጣትና መግባት››ና ‹‹እንቅልፍና እድሜ›› የተሰኙ መፃሐፎቹን ደጋግሜ አነባለሁ፡፡ከ‹‹አሜን ባሻገር››ን ሳነበም ሁለት ነገሮች እንደ እብድ ብቻየን እንድስቅ አስገድደውኛል፡፡አንደኛው የበረራ አስተናጋጆች(ወይም በወንበሩ በተገጠሙት ስክሪኖች አማካኝነት የሚታየው መመርያ) በአደጋ ጊዜ እንደህ አድርጉ እንድያ በሉ እያሉ ተጓዦችን የሚያስቡኩበት ክፍለ ጊዜ የገለፀበት ፅሑፍ ላይ፣

‹‹ለመሆኑ በአደጋ ሰዓት ከወንበሬ ስር መንሳፈፍያ ከረጢት መኖር አለመኖሩን ይቅርና፣ ወንበር ላይ ልቀመጥ ጉቶ ላይ እንዴት ትዝ ሊለኝ ይችላል? ሰው አለቅጥ ሲደነግጥ እንዲህ ያለውን የጥንቃቄ ዝርዝር ይቅርና በሽንት ቤት እና በሱሪው መካከል ያለውን ልዩነት እንኳን ይረሳዋል፡፡ለዚህ ነው ብዙ ደንጉጦች በአደጋ ሰዓት ሽንታቸውን ለሱሪያቸው የሚያስረክቡት፡፡›› የሚለውን ሳነብ በጣም ስቄያለሁ፡፡ አሁንም እየሳቅኩኝ ነው የምፅፈው፡፡(ገፅ 41)

ሌላው በጣም ያሳቀኝ ደሞ፣ በቢላደን ምክንያት ፂማም ሰዎች ሁሉ አሸባሪዎች እንደሚመስሉት ይገልጥና፣ ካጠገቡ የተቀመጠው ፂማም ተሳፋሪም አሸባሪ እንዳይሆን ስለጠረጠረ ሰውየው ‹‹ጠብደል ከመሆኑ የተነሳ›› አውሮፕላንዋን አንዳይጠልፋት መስጋቱን ይተርካል፡፡ከዛም፣ ያ አሸባሪ ሊሆን ይችላል ብሎ የገመተው ሰውዬ አውሮፕላንዋን ሳይሆን ሽንት ቤቱን መጥለፉ( ሽንት ቤት ውስጥ በጣም መቆየቱን) ይታዘባል፡፡ያኔ፣ ‹‹ሰውዬው ኑሮውን ነው እንዴ የሚፀዳዳው?›› የሚለውን መስመር ሳነብ በሳቅ ፍርስ ብያለሁ፡፡(ገፅ 43)

የስነ ግጥም ጥበብ መግጠሙ ላይ ብቻ ሳይሆን አነባበቡም የተለየ ተሰጥኦና ክህሎት የሚጠይቅ ይመስለኛል፡፡ለዛም ሳይሆን አይቀርም በሃገራችን በገጣሚነታቸው ወደር የለሽና አንቱ የተባሉ ገጣሚዎች የገጠሙት ግጥም ራሴ ሳነበው ያን ያህል ስሜት አይሰጠኝም፡፡በተለይ ግጥሙ በጣም ረዥም ከሆነ፣ያለወትሮየ እንቅልፍ እንቅልፍ ይለኛል፤ አሁንም አሁንም ያፋሽገኛል፡፡እናም ሳልጨርሰው በጅምር ይቀራል፡፡ገጣሚዎቹ ሲያንቆረቁሩት ማዳመጥ ግን የሆነ ለመግለፁ የሚከብደኝ የመንፈስ ልዕልና ይሰማኛል፡፡

የበውቀቱ አጫጭር ግጥሞች ግን ከዚህ የተለዩ ሆኖው አግቻቸዋለሁ፡፡ገጣሚው ሲያነባቸውም ሆነ ራሴ ሳነባቸው፣ ህሊናየን እንደ ምግብ ያጠግቧታል፣ ለነብሴም መድሓኒት ሆኖው ይፈውሷታል፡፡ራሱ የገጠማቸው ግጥሞች ብቻም ሳይሆን የሚፅፋቸው መጣጥፎች ጥልቅ የሆነ መልእክት እንዲያስተላልፉለት የሚመርጣቸው ግጥሞችም አስደናቂ ናቸው፡፡

Friday, February 12, 2016

‹‹ለአፍሪካውያን ዲሞክራሲ ቅንጦት ነው›› አትሌት ኃይለ ገብረስላሴ


እውቁ አትሌት ኃይለ ገብረስላሴ ‹‹ለፍሪካውያን በጣም ወሳኙ ነገር ዲሞክራሲ ሳይሆን ጥሩ ገዢ ነው፤ እንዲህ ሲሆን ነው አህጉሪቱ ልትለወጥ የምትችለው፡፡ካልሆነ ግን በፍፁም ልትለወጥ አትችልም›› ያለው ለቢቢሲ በሰጠው ቃለ መጠይቅ ላይ ነው፡፡

በአሁኑ ወቅት 1,700 ሰራተኞች እንዳሉትና በሪልስቴት ጀምሮ በስፖርት ማዘውተርያ፣ ስኒማ ቤት፣ መኪና ድለላ፣ሆቴል፣ ሪዞርት፣ የቡና እርሻ እያለ በወርቅ ቁፋሮ እስከ መሰማራት እንደደረሰ የሚገልፀው አትሌቱ፣ ጋዜጠኛው የዓለም ባንክ ያወጣው ሪፕርትን ጠቅሶ ‹‹በኢትዮጵያ መዋዕለ ንዋይ ፈሰስ ማድረግ ከባድ ነው፤ችግሮች ያጋጥሙሃል?›› ብሎ ሲጠይቀው፤

ይህን የሚያደርገው ብዙ ሰዎች እንደሚሉት በውጭ ሃገራት መዋዕለ ንዋዩን ለማፍሰስ ዕድል እንዳለው ነገር ግን ‹‹ይህ ሃገሬ ነው፤ እችው ነች እናቴ…በሃገሬ ኢንቨስት በማድረግ ቅድምያውን በመውሰድ ለሌሎች አርአያ መሆን እፈልጋለሁ›› ብሏል፡፡ በመቀጠልም ‹‹እናትህ መጥፎ ብትሆን አናቴ አይደለሽም ማለት ትችላለህ?›› በማለት ጥያቄውን በጥያቄ መልሶለታል፡፡
‹‹ብዙ ሰዎች ዲሞክራሲ ያስፈልገናል ይላሉ፤ አንተ ለምን ዲሞክራሲ አያስፈልግም ትላለህ?›› የሚለው ጥያቄ ሲመልስ ‹‹እንዲህ በማለቴ አዝናለሁ፡፡በእርግጥ፣ ዲሞክራሲ ያስፈልገናል፤ነገር ግን፣ መቅደም ያለበት የትኛው ነው? ሁሌም ዲሞክራሲ ዲሞክራሲ እንላለን…ግን ዲሞክራሲ በመጠኑም ቢሆን ቀንጦት ነው›› ብሏል፡፡

በ2010 ዓ.ም በሚካሄደው ሃገራዊ ምርጫ ሊወዳደር እንደሚችል ፍንጭ የሰጠው አትሌት ሃይለ ለ25 ዓመታት ዓለምን ዞሮ ያካበተው ልምድ ቀላል እንዳልሆነና ይህንን ልምዱን ለሃገሩ በሚጠቅም መልኩ የሚያካፍለው በፕረዚዳንትነት፣ በጠቅላይ ሚኒስተርነት ይሁን በሚኒስተርነት ግን ወደፊት የሚታይ ይሆናል ብሏል፡፡

ተወዳጁ አትሌት ሃይለ ገብረስላሴ ‹‹ዲሞክራሲ ለአፍሪካውያን ቅንጦት ነው›› በማለቱ ብዙ ፌስቡክ ተጠቃሚ ኢትዮጵያውያን ሳይበሳጩበት አልቀሩም፡፡የአንዳንዶቹን አስተያየትና ግብረመልስ እንደሚከተለው ቀርቧል፡፡ እርሶስ ምን ይላሉ? መልካም ንባብ፡፡


Wednesday, February 10, 2016

ኢቲቪ(ኢቢሲ) ከርሞ ጥጃ የሆነባቸው ምክንያቶች


1. በኢትዮጵያ የመደብ እንጂ የስርዓት ለውጥ
ስላልተከሰተባለፉት 50 ዓመታት መከታተል ኢትዮጰያን በሐይል ተቆጣጥረው ያስተዳደሩ ገዢዎች ከሞላ ጎደል ተቃራራቢ ናቸው፡፡ዘላለም ክብረት በቅርቡ ያደረገው ዳሰሳ የሚያመለክተው ሶስቱም ገዢዎች( ዘውዳዊው፣ ወታደራዊውና ኢህአዴግ) በአምባገነንነት እንደሚታወቁ ነው [1]፡፡ፅሑፎ የሚያመለክተው ከሶስቱም ገዢዎች በአፋኝነት የከፋው ደርግ ሲሆን ዘውዳዊውና የኢህአዴግ አገዛዝ በትንሹ ይሻላሉ፡፡ዘውዳዊው አገዛዝ ለመውደቅ ሲቃረብ ኢህአዴግ ደሞ በመጀመርያው አስር ዓመታት ደህና ነበሩ፡፡ያም ሆኖ ግን ልዩነታቸው እስከዚህም እንዳልነበር ነው፡፡ይህ ከሆነ ታድያ፣ አምባገነኖች ያለምንም ገደብ የፈለጉትን ይናገራሉ፣ ያደርጋሉ እንጂ የህዝብ ፍላጎት ብሎ ነገር አይውቁም፡፡ህዝቡ በኢቲቪ/ኢቢሲ ዝግጅቶች ደስተኛ ባይሆንም እንደ ኮሶ ቋቅ እስኪለው ድረስ ይግቱታል እንጂ የአቀራረብም ሆነ የይዘት ለውጥ ለማድረግ አይጨነቁም፡፡በለላ አነጋገር የኢቢሲ ኦዲቶርያል ፖሊሲ ከገዢው መደብ ጥቅምና ፍላጎት የሚመነጭ ነው፡፡
2. በጥናት ሳይሆን በትእዛዝ የሚመራ ስለሆነ

ከላይ እንደተጠቀሰው የኢቢሲ ግብ ሃገራዊ ሳይሆን የገዢው መደብ ጥቅምና ፍላጎት ማስጠበቅና ዓላማዎቹን ከግብ ማድረስ ነው፡፡ዋና ግቡ ቡዱናዊ ከሆነ እንግዲህ ድርጅቱ የሚመራው በጥናትና ምርምር ሳይሆን በትእዛዝ እንዲሆን ይገደዳል ማለት ነው፡፡ለዛውም ነው ባለፉት 50 ዓመታት ተመሳሳይ ተግባራት ሲፈፅም የሚስተዋለው፡፡በሌላ አገላለፅ የሃገራችን የፖለቲካ ሙቀት የሚለካው በኢቲቪ/ኢቢሲ ነው፡፡በጣም ሲግል ሌሎች ዝግጅቶች ዘግቶ የአዛዦቹን የደም ፍላት ሲንፈቀፈቅ ያሳያል፤አዛዦቹ አሁንም አሁንም በሞስኮቱ ብቅ እያሉ ሲደነፉና ሲገለፍጡ ያመለክታል፤ በጣም ሲቀዘቅዝ ደሞ ዜናውም ጭምር ድራማና ማስታወቅያ ይሆናል፡፡ኢቲቪ/ኢቢሲ በእነዚህ ጊዚያት ብቻ ነው ብዙ ተከታታዮች የሚያገኘው፡፡በአመፅ፣በጦርነትና ህዝቡ ተስፋ ሲቆርጥና አማራጭ ሲያጣ ተመልካች ይስባል፡፡

ህዝቡ አማራጭ ሲያጣ ጋዜጠኞቹም አማራጭ ስለሚያጡ ነው መሰለኝ አንድ ነገር ዓመት ሙሉ እየደጋገሙ ይዘግቡታል፡፡ለምሳሌ አንድ ዩኒቨርሲቲ ሊሰራ ሲታሰብ ስለመታሰቡ ይዘግባል፡፡በሚቀጥሉት አምስት ዓመታት ዩኒቨርሲቲ ሊሰራ ታስቧል ይባላል፡፡ከዛም የመሰረት ድንጋይ ሲቀመጥ ይዘገባል፡፡ቁፋሮ ሲጀመር ይዘግባል፣ ቁራሮው ሲያልቅ ይዘግባል፣ግንባታ ሲጀመር ግንባታ መጀመሩን ያበስራል፣ግንባታው 10 ከመቶ ሲደርስ ይህንኑ ያስውቃል፣ከርሞ ከርሞ 15 ፐርሰንት ተጠናቅቋል ይላል፣ደሞ ቆይቶ ቆይቶ ቆይቶ 20 ፐርሰንት ደርሷል ይላል፣ እንደገና ከተረሳ በኋላ 25 ፐርሰንት ደረሰ ይላል፣30 ፐርሰነት…እያለ እያለ እያለ ከስንት ዓመታት በኋላ 90 ፐርሰንት ሲደርስ ለምርቃት ይዘግባል፡፡ደሞ ለተማሪዎች ምዝገባ ይዘግባል…ለታማሪዎች ምርቃት ይዘግባል…የተመረቁ ተማሪዎች በጥቃቅንና አነስተኛ ተደራጅተው ኮብል ስቶን ሲጠርቡ ያሳያል…

በጥናት የሚመራ ቢሆን ኖሮ ግን የቁጥጥር፣የይዘት፣ሚዲያው የሚጠቀምበት ቴክኖሎጂ፣የተመልካች፣የዓላማ(ግብ)ና የሁኔታ ትንታኔዎችና ግምገማዎችን በየጊዜው በማድረግ፣ዳስሳዎችንና ጥልቅ ጥናቶችን በማካሄድ ከዘመኑ ጋራ መራመድ ይችል ነበር፡፡በኢቲቪ/ኢቢሲ እምነት ከ50 ዓመታት በፊት የነበረው የኢትዮጵያ ህዝብ ዛሬም ያውና እኩል ነው፡፡የቴሌቪዥን መስኮቶች ከለር እንኳን ጥቁር ሁሉም ዓይነት ከለሮች(ቀለሞች) እስከሟሟላት፣ ከድቡልቡልና ጠፍጣፋ ወደ ፍላት ስክሪን ማደጉን ልብ ያለ አይመስልም፡፡በጣም የሚገርመው ግን ህዝቡ ከምሳና እራቱን ቆጥቦ ዲሽ መግዛቱ በኢቲቪ/ኢቢሲ መሰላቸቱ ሳይሆን ሃገሪቱ ያስመዘገበችው ፈጣን እድገት ማሳያ ነው ብለው ማሰባቸውን ነው፡፡

ኢቲቪ/ኢቢሲ ይህ በመሆኑ በጣም በተደጋጋሚ የተጎዳው ኢህአዴግ ብቻ ነው፡፡ለምን?@Andualem Buketo Geda ን ጠይቁት፤ እንዲህ ይላል…
‹‹…እኔ እስከምረዳዉ እንደ ኢቲቪ ዋና የወያኔ ጥላት የለም …..እንግዲህ አብዛኛዎቻችን ወያኔን ጠልተን የቀረነዉ በፌስቡክ ተነግሮን አልነበረም መቼም….. እንደ ኢቲቪ ስለወያኔ አስከፊነት በመንገር ሆዳችንን የሞላን ነበረ እንዴ?!….በነገራችን ላይ ኢቲቪ ያኔ ወያኔ ጫካ እያለች እንድትጠላ ሲሰራ የነበረዉ ፕሮፓጋንዳ የተሳካ ሲሆን አሁን ደግሞ ስልጣን ከያዘች በኋላ ስለልማትም ይሁን ስለጥፋት በሚያቀርባቸዉ አሰልቺ ፕሮፓጋንዳዎች ወያኔ ተጠልታ እንድትቀር አሌ የሚባል አስተዋጽኦ እያደረገ ይገኛል፡፡ቴንክ ዩ ኢቲቪ የትግላችን አጋር ነህ…..›› [2]
ኢቲቪ/ኢቢሰ በጣም ተሸወደው ግን…
3. የኢትዮጵያ ህዝብ አንድ አንድ የአዲስ አበባ ኗሪዎች ስለሚመስለው ነው

አንድ አንድ የአዲስ አበባ
ኗሪዎች ሁሉ ጊዜ ኢቲቪ/ኢቢሲ ይከታተላሉ፡፡ምክንያቱም፣ ተናገሩ እያለ ስለሚወተውታቸውና ያልተናገሩት ነገር ተናግሯል ብሎ ካስተላለፈ ሰፈር ለመቀየር ወይም ሃገር ጥለው ለመሸሽ እንዲዘጋጁ ነው፡፡ለዛም ነው አንድ አንድ የአዲስ አበባ ኗሪዎች ሰፈራቸው የት እንደሆነ የማይታወቁት፡፡ስለዚህ ኢቲቪ/ኢቢሲ ምን እንደሚዘግብ፣ለምን ምክንያት እንደሚዘግብ፣በምን ሁኔታ ተመስርቶ እንደሚዘግብ፣እንዴት እንደሚያሰራጨው፣መቼና ለማን እንደሚያቀርበው፣ የዘገባው ውጤት ምን እንደሆነ አያውቅም ማለት ነው፡፡በርግጥ መገመቱ አይቀርም…ግምቱ ግን የጥንቆላ ያህል ነው፡፡ልክ በአየር ሁኔታ(ሜትሮሎጂ) ስዓት እንደሚያቀርበው ግምት ማለት ነው፡፡

[1] Zelalem Kibret, ዴሞክራሲ በኢትዮጵያ፡ የግማሽ ምዕተ ዓመት ጉዞhttps://www.facebook.com/notes/zone9/%E1%8B%B4%E1%88%9E%E1%8A%AD%E1%88%AB%E1%88%B2-%E1%89%A0%E1%8A%A2%E1%89%B5%E1%8B%AE%E1%8C%B5%E1%8B%AB-%E1%8B%A8%E1%8C%8D%E1%88%9B%E1%88%BD-%E1%88%9D%E1%8B%95%E1%89%B0-%E1%8B%93%E1%88%98%E1%89%B5-%E1%8C%89%E1%8B%9E/935633566525136[2] Andualem Buketo, ሶልሻየር,https://www.facebook.com/andualem.geda/posts/10153581859854915

Saturday, February 6, 2016

ወይ አዲስ አበባ...አበባ ወይ አራዳ ሆይ ዙርያሽ አቢዪ


ወይ አዲስ አበባ...አበባ ወይ አራዳ ሆይ
ሃገርም እንደ ሰው እንደ ሰው ይናፍቃል ወይ

ትላለች ድምፃዊት ዙርያሽ አቢዪ፡፡


‹‹አራዳ›› በአንጋፋው ደምፃዊ ዳዊት ፅጌ

በአንጋፋው ደምፃዊ ዳዊት ፅጌ የተዘፈነው ‹‹አራዳ›› የተሰኘ ዘመን ተሻጋሪ ዜማ ተጋበዙልን፡፡አስተያየታችሁና ስሜታችሁ ብታካፍሉን በደስታ እንቀበላለን፡፡


Sunday, January 31, 2016

ዛሬ ልደቴ ነው፤ በእውነት እንኳንም ተወለድኩ!



‹‹እኳን ተወለድክ፤ መልካም የልደት ቀን ይሁንልህ፤ቀሪው ህይወትህ የስኬትና የደስታ ያድርግልህ፣ HBD፣Happy Birthday፣…ወዘተ›› እያላችሁ ያሸበረቁና የደመቁ የመልካም ልደት ፖስት ካርዶች እንዲሁም መልካም ልደት የሚል ፅሑፍ ያላቸው የተለያዩ ዓይነት ኬኮች በውስጥ መስመር በምስል ልካችሁ ምራቄን ያስዋጣችሁኝ ውድ ጓደኞቼን በጣም አመሰግናለሁ፡፡አዎ፣ እውነት ነው፤ ለክፉም ለደጉም እኳንም ተወለድኩ፡፡የኑሮ ምሬት ‹‹ምነው ባልተወድኩ›› ብዬ እንዳማርር፣ አንዳንዴም ራሴን ለማጥፋት እንዳስብ ያደረገኝ ጊዚያቶች እንዳሉ ሁሉ፣ ‹‹ዋው! ኧረ እንኳን ተወደልድኩ…ኧረ በስሜት ተገፋፍቼ እንኳን ራሴን አላጠፋሁ›› ያልኳቸው ምክንያቶችና ቀኖችም አሉ፡፡

በዚህች ዓለም ስኖር ሶስት ዓይነት ሰዎች አጋጥመውኛል፡፡የመጀርያዎቹ ለከፍተኛ አደጋ ዳርገውኛል…የመኖርና ያለመኖር የህይወት ጥያቄዎችን እንዳስተናግድ አስገድደውኛል፡፡የመኖር ፈተና ከብዶኝ ለመውደቅ ስንገዳገድ ወደማልወጣው አዘቅት ገፍትረውኛል፡፡ክፉ ስለሆንኩኝ ግን አልነበረም፡፡ብቻ፣ እንደ ሰው መኖሬን ያበገናቸው፣ ስያዩኝ ደም ደም የሚሸታቸው ነበሩ፡፡ሁለተኛዎቹ የመጀመርያዎቹ ከደቀኑበኝ የመኖርና ያለመኖር አደጋ የታደጉኝ የህይወቴ መድህን ናቸው፡፡በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ እስከዛሬ ድረስ እንድኖር ረድተውኛል፡፡ጥላ ከለላ ሆኖውኛል፣ ሳዝን አፅናንተውኛል፣ ተስፋ ስቆርጥ አበረታተውኛል፣ ተዳክሜ ለመውደቅ ስንገዳገድ ደግፈውኛል…ቁሜ እንድራመድ ረድተውኛል፡፡ሶስተኛዎቹ አልፎ ሂያጆች ናቸው…አልጎዱኝም፤ አልጠቀሙኝምም፡፡ምናልባት ግን፣ በተዘዋዋሪ ጠቅመውኝም ጎድተውኝም ሊሆን ይችላል፡፡
በህይወቴ አለኝ የምለው፣ ምንጊዜም የሚያስደስተኝ፣ ሳዝን የሚያፅናናኝ፣ ቀን ሲጎድልብኝና የተስፋ ወገቤን ሲያጎብጠኝ ተስፋ የሚያሰንቀኝ፣ ፍረድሪክ ኒች ‹‹That doesn’t kill you makes you stronger››(የማይገድሉ ፈታኝ አጋጣሚዎች ይበልጥ ያጠነክሩሃል) እንዳለው የመኖር ዕዳና ሸክም ካቅሜ በላይ ሆኖ ከሚሰብረኝ ይልቅ ይበልጥ እንዲያጠነክረኝ የረዳኝ ብቸኛው ስጦታየ የንባብ ችሎታየ ነው፡፡ለማንበብ ያለኝ ፍቅርና ጉጉት ወደር የለውም፡፡ሱስ የለው፣ ጭስ የለው፣ ድካምና ጭንቀት የለው፣ ፀፀትና ቁጭት የለው…ደስታ ብቻ፡፡ብዙ አሳዛኝ ልበ ወለዶችና እውነተኛ ታሪኮች አንበቤያለሁ፡፡ሆኖም ግን፣ ለካ እንዲህም አለ? ብየ ከመገረምና ከመደነቅ አልፌ በማንበቤ የተቆጨሁበት ቀን የለም፡፡ይልቅኑስ፣ የሚነበብ ፍለጋ እሰማራለሁ፡፡በጣም የጠቀሙኝ ሰዎች እንግዲህ ማንበብ እንድችልና የሚነበብ እንዳላጣ የረዱኝ፣ በተአምረኛ የአፃፃፍ ችሎታቸው ቀልቤን ስበው አድናቄያቸው እንድሆን ያደረጉኝና እያደረጉኝ ያሉት ናቸው፡፡
‹‹ዋው! ኧረ እንኳን ተወደልድኩ…ኧረ በስሜት ተገፋፍቼ እንኳን እራሴን አላጠፋሁ›› ካስባሉኝ ምክንያቶች አንዱ በአካል ሳይሆን በንባብ የተዋወቅኳቸውና የዚህች ዓለም ብርሃን እንዳላይ የጋረደኝ የአመለካከት ግርዶሽ ያለ ምንም ስቃይና ጠባሳ በቀዶ ጥገና ያስወገዱልኝ የተለያዩ ዓይነት ደራሲዎች ናቸው፡፡በተለይ እማ ስለህይወትና ስለሰው የሚፅፉ የጥበብ ዕንቆች፡፡

Sunday, November 29, 2015

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ በድርቁ የተጠቃው የኢትዮጵያ ህዝብ ብዛት ‹‹20 ሚሊዮን ሊሆን ይችላል›› አሉ


Ø  ‹‹በኢትዮጵያ ውስጥ በእንዲህ ዓይነት ስፋት ድርቅ ተከስቶ አያውቅም››

Ø  ‹‹ከአየር ንብረቱ መዛባት ጋር ተያይዞ ብዙ ቦታዎች ላይ ያሉ ግድቦቻችን በከፍተኛ ደረጃ ቀንሰዋል፡፡››

  Ø‹‹ስለዚህ ድርቁ ራሱ በፈጠረው የውኃ ችግር የኤሌክትሪክ እጥረት አጋጥሟል፡፡››

Ø‹‹በድርቁ የተጠቃው የህዝብ ብዛት እየተጠና ነው፤ ‹‹አሥራ አምስት ሚሊዮንም ሊሆን ይችላል፤ ሃያ ሚሊዮን ሊሆን ይችላል፡፡››

Ø  ‹‹መጀመሪያዎቹ አካባቢ ከውጭ ያስገባነው ወደ 250 ሺሕ ሜትሪክ ቶን እህል ነበር፡፡ አሁን ግን ተጨማሪ 650 ሺሕ ሜትሪክ ቶን እህል እንደገና አዘናል፡፡››

Ø  ‹‹የአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ገና ተግባራዊ አልሆነም፡፡ አዲስ አበባ የራሷ ድንበር አላት፡፡ ከድንበሩ አንድ ኢንች ወደ ኦሮሚያ አትገባም፡፡››

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ


ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ከሪፖርተር ጋርባደረጉት ረዘም ያለ ቃለ መጠይቅ ድርቁ ያስከተላቸው መጠነ ሰፊ ችግሮችን ይፋ አድርጓል፡፡ጠቅላይ ሚኒትሩ ባሃገራችን ከሚገኙ የግል መገናኛ ብዙሐን ቃለ መጠይቅ ሲያደርጉ የመጀመርያቸው ሲሆን በኢትዮጵያ የተከሰተው እጅግ አደገኛ ድርቅ የሃገሪቱ አንድ አራተኛ የሚሆነውን ህዝብ ለተረጅነት ሊዳርግ እንደሚችልና የግድቦች የውሃ መጠን በጣም በመቀነሱ ምክንያት ከፍተኛ የኤሌክትሪክ ዕጥረት ማስከተሉን ተናግሯል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ዘንድሮ የተከሰተው ድርቅ ‹‹በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ ከተከሰተው ድርቅ ሰፋ ያለና›› አብዛኛው የሃገሪቱ ክፍል ያካለለ በመሆኑ የተረጂዎች ቁጥር ሊያሻቅብ እንደሚችል ገልፀዋል፡፡‹‹ማንም የማይቆጣጠረው ሰፊ አካባቢ በድርቁ ተጠቅቷል፡፡›› ያሉት ሚኒስትሩ ‹‹ቁጥሩ ምን ይሁን ምን በሒደት የሚወሰን ነው፡፡ አሥራ አምስት ሚሊዮንም ሊሆን ይችላል፤ ሃያ ሚሊዮን ሊሆን ይችላል፡፡ እኛ ብዙ ትኩረት የምንሰጠው ቁጥሩ ላይ አይደለም፡፡ ዋናው ግን እኛ እያደረግን ያለነው እያንዳንዱ ቤተሰብ ምን ደረጃ ላይ ነው? የሚለው ነው›› ሲሉም አስተያየታቸውን አክሏል፡፡

‹‹ሌብነት የለመደ በአንድ ሳምንት ውስጥ ቴሌቪዥን ላይ ወጥተን ስለጮህን እጁን ይሰበስባል ማለት አይደለም›› ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ


ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንዲህ ዓይነት ቆይታ ከግል የኅትመት ሚዲያ ጋር ሲያደርጉ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በቆይታቸውም ወቅታዊ በሆኑ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች ላይ ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡ በቅርቡ ከተከሰተው ድርቅ አንስቶ ስለመልካም አስተዳደር ችግሮች፣ እንዲሁም በኤርትራ ጉዳይ ላይ ያደረጉት ልዩ ቃለ ምልልስ እንደሚከተለው ቀርቧል፡፡  
ሪፖርተር፡- ከኤልኒኖ ጋር በተያያዘ በአገሪቱ የተለያዩ ክልሎች ድርቅ መከሰቱ ይታወቃል፡፡ እስካሁን ድረስ ዕርዳታ የሚያስፈልጋቸው ዜጎች ቁጥር 8.2 ሚሊዮን መድረሱን መንግሥት አስታውቆ ነበር፡፡ ሆኖም ግን ዓለም አቀፍ የዕርዳታ ድርጅቶች የተረጂዎቹ ቁጥር 15 ሚሊዮን እንደሚደርስ እየተናገሩ ነው፡፡ በተጓዳኝ ደግሞ ከለጋሾች የሚጠበቀው ዕርዳታ በተጠበቀው መጠን እየተገኘ አይደለም፡፡ ስለዚህ ነገሮች በዚሁ ከቀጠሉ መንግሥት ጉዳዩን እንዴት ለመወጣት አስቧል? የሚታጠፉ የመንግሥት ፕሮጀክቶች አሉ ብለዋል፡፡ የትኞቹ ናቸው? የአገሪቱ የአደጋ መከላከል ዝግጁነት ምን ይመስላል? በተለይ ከዚህ ድርቅ ጋር ተያይዞ የሚነሳው ጥያቄ ተጎጂዎች ዕርዳታው በአግባቡ እየደረሳቸው አለመሆኑን ነው፡፡ እኛም በቦታ ላይ ተገኝተን ይህን መታዘብ ችለናል፡፡ ስለዚህ በድርቁ የተጎዱ ወገኖችን የመርዳቱ ሒደት ቅንጅት የጎደለው ነው ይባላል? እዚህ ላይ ምን ይላሉ?

Tuesday, September 1, 2015

አእምሮ የሌለው ሕዝብ…( ነጋድራሰ ገብረ ሕይወት ባይከዳኝ፣ ስራዎች)




የባለ ምጥቁ አእምሮአርቆ አሳቢእጅግ ታላቅ ሰው...የገብረ ሕይወት ባይዳኝ ስራዎችን እስካሁን ባለማንበቤ ምንኛ ቆጨኝ መሰላችሁ፡፡እስኪ፣ እርሳቸው ከፃፏቸው ያስገረሙኝን ቃል በቃል ላካፍላችሁእንደኔ ያላነበባችሁ ጓደኞቼ በእርግጠኝነት ትገረማላችሁ፡፡ እርሳቸው ይህን ከፃፉት አንድ መቶ ዓመታት( አንድ ክፍለ ዘመን) እንደ ጉድ እብስ ብሏል፡፡ያም ሆኖ ግን፣ የእርሳቸው ወርቃማ ምክሮች ዛሬም ድረስ ተግባራዊ ሆኗል ብየ ለመናገር ያስቸግረኛል፡፡
‹‹ምነው የኢትዮጵያ ሕዝብ ከእንቅልፍህ መቸ ትነሳለህ? በዓለም ላይ የሚደረገውን ነገር ለማየትስ ዓይንሀን መቸ ትከፍታለህ?
አእምሮ በአእምሮ ካልሆነ በቀር በሌላ አትታገድም፡፡ስለዚህ ወዮለጽ በድንቁርና ለሚቀመጥ ሕዝብ ውሎ አድሮ ይደመሰሳልና፡፡››(ገፅ 22)
መንግስታችንም እንድትቀና የሚከተሉት አስር ነገሮች በቶሎ ቢፈፀሙ ማለፍያ ነበር፡፡
1.
ለመንግስት የሚሆን ገንዘብና ለንጉሱ የሚሆነውን ገንዘብ በስርዓት ይለይ
2.
ሕዝቡ ለመንግስት የሚከፍለው ግብር እንደየሀብቱ መጠን ቁጥር ሁኖ ይታወቅለት
3.
ሕዝቡም የሚከፍለው ግብር በብር እንጂ በእህል፣ በማርም በፍሪዳም አይሁን፡፡የመንግስት ስራ ሁሉም በባላገር አይሰራ፤ በባለ ደሞዝ እንጂ፡፡
4.
የአማርኛ ቋንቋ ገና ስዋስው አልተበጀለትም፡፡ ስለዚህ መንግስታችን ከያገሩ ስዋስው የሚያውቁትን ሊቃውንት ሰብስቦ ያማርኛን ቋንቋ ስዋስው ቢያስወጣ ደግ ነው፡፡
5.
ፍትሐ ነገስታችን ከዛሬው ያደባባይ ስርዓት ጋር አይስማማም፡፡ስለዚህ መንግስት የስርዓት አዋቂዎችን ሰብስቦ ከኤሮጳ ስርዓት ጋር የተስማማ ፍትሐ ነገስት ያውጣ፡፡የተፃፈ ስርዓት የሌለው መንግስት ብዙ ዕድሜ የለውም፡፡
6.
ያገራችን ሰራዊት ስርዓት የለውም፡፡ ስለዚህ የኤሮጳን መኳንንት አምጥተው ሰልፍን ቢማር ማለፍያ ነበር፡፡
7.
የዛሬው የመንግስታችን ብር የተበላሸ ና፡፡ ስርዓት ውል የለውም፡፡ባንዱም አውራጃ በጨው በሌላው በጥይት የሰፈራል፡፡
8.
ላገራችን ነጋዴ ስርዓት እስኪወጣለት ድረስ መንግስታችን አይቀናም፡፡
9.
ሕዝቡ ባንድ መንግስት ውስጥ መሆኑን አጥብቆ እንዲያውቀው አገሩን የሚዞሩ ተቆጣጣሪዎች ይሸሙበት፡፡
10.
የሃይማኖት አርነት ይታወጅ፡፡የሃይማኖት አርነት ጥቅም መሆኑን የማያውቅ ብዙ ሰው ይኖራል፡፡ያገራችን ሰው የተዋህዶ ሃይማኖት ከሁሉ ሃይማኖት ይበልጣል ብሎ ያምናል፡፡ በልጦ ግን ምን ረባን? ማንስ አወቀው? …ደግሞም ባገራችን አንድ የድንቁርና ነገር አለ፡፡ ሃይማኖቱ ተዋህዶ ያልሆነ ሰው አንደ ርኩስ ይቆጠራል፡፡ይህም እጅግ ያስቃል፡፡ አእምሮ የሌለው ሕዝብ ሁሉ የእግዚአብሔርን ቃል ሳያውቅ የእግዚአብሔር ጠበቃ ሊሆን ይወዳል፡፡
ሃይማኖት የልብ ነገር ነው፡፡ስለዚህ ሰማያዊው ንጉስ እንጂ የዚህ ዓለም ንጉስ አይቆጣጠረውም፡፡(ገፅ 23-28)
በአጠቃላይ፣ አእመሮ የሌለው ሕዝብ የሚከተሉትን ወሳኝ ነገሮች አይኖሩትም፡፡