ህወሓት የተመሰረተበት 40ኛው ዓመት የተከበረበት ቀንን ተንተርሰው የብአዴኑ አመራር አቶ በረከት
ስምኦንና የህወሓቱ ከፍተኛ አመራር አቦይ ስብሓት ነጋ ስለመለስ የሰጧቸው አስተያየቶች አነጋጋሪ ሆኗል፡፡ፌስቡክን ጨምሮ የማሕበራዊ
ድረገፆች ተጠቃሚዎች ሲቀባበሏቸው ሰንብቷለ፤ የየራሳቸው አስተያየቶችም ሰጥተውባቸዋል፡፡ከፊሎቹ በረከት ነው ትክክል ሲሉ፣ ከፊሎቹ
ደሞ አይ አቦይ ስብሓት ናቸው ትክክል ሲሉም ተስተውሏል፡፡ለማስታወስ ያህል ሁለቱም የኢህአዴግ አመራሮች የሰጥዋቸው አስተያየቶች
እንሆ፡
አቶ በረከት ስምኦን‹‹
መለስ በክፍለ ዘመን አንዴ ከሚፈጠሩ ሰዎች የሚመደብ ነው›› ሲሉ፣ አቶ ስብሐት ነጋ
በበኩላቸው ‹‹የለም፣ አሁኑኑ ብዙ መለሶች መፈጠር ይችላሉ›› በማለት የአቶ በረከት አስተያየት እንደተቃወሙት ሪፖርተር ጋዜጣ ሳይቀር ዘግቦታል፡፡ለመሆኑ እነዚህ አስተያየቶች ልዩነት አላቸው? ካላቸው፣ ልዩነቱ ምንድን ነው? አንድነታቸውስ ምን ድን ነው? እስኪ የቻልነውን ያህል በጥልቀት እንመርምራቸውና ከአምልኮተ መለስ
ጋራ ያላቸው ዝምድና ለማየት እንሞክር፡፡
ሁለቱም አስተያየቶች በጥንቃቄ ስንመረምራቸው ያን ያህል የጎላ ልዩነት የላቸውም፡፡አቶ በረከት ያሉት መለስን የመሰለ መሪ ለማፍራት ብያንስ አንድ ክፍለ ዘመን ይወስዳል ሲሆን አቦይ ስብሓት ግን አሁኑኑ ብዙ መለሶች መፍጠር ይቻላል ነው ያሉት፡፡በመሆኑም በሁለቱም አስተያየቶች ያለው ልዩነት የጊዜው ማጠርና መርዘም ብቻ ነው፡፡
በተረፈ ግን፣ ሁለቱም መለስን ከማድነቅ አልፈው አምላኪዎች መሆናቸውን አሌ የሚባል አይደለም፡፡የሁለቱም ፍላጎትና ፀሎት መለስን የመሰለ ‹‹መሪ›› በማፍራት ላይ ያጠነጥናል፡፡ሁለቱም በመለስ ፍፁምነት ያምናሉ፤ እንደ ጣኦት ያመልካሉ፡፡መለስን በሌላ ‹‹መሪ›› መለወጥ ማለት ሃይማኖት የመለወጥ ያህል ይቆጥሩታል፡፡በመለስ ላይ ያላቸው እይታ
ምክንያታዊ ሳይሆን በጭፍን ስሜታዊነት የታወረ ነው፡፡ለዛም ነው መለስ የማይካዱ ጠንካራ ጎኖች እንደነበሩት ሁሉ፣ ማንም በቀላሉ
የማይረሳቸው የዘቀጡ ስራዎች ማከናወኑም ግልፅ ሆኖ ሳለ እነሱ ግን ማስተዋል የተሳናቸው፡፡